አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ — አማራ ባንክ በደብረ ብርሃን ከተማና አካባቢው ከሚገኙ ደንበኞች፣ ባለሀብቶች፣ ባለድርሻ አካላት እና ከሌሎች ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሁለት ቀናት የቆየ ውይይት አካሄደ።
ውይይቱ የባንኩን አገልግሎት ማሻሻል፣ ከደንበኞችና ከባለድርሻ አካላት ጋር ያለውን ግንኙነት ማጠናከር እና የጋራ ዕድገት አቅጣጫዎችን ለመለየት ያስቻለ ነበር ተብሏል።
በውይይቱ ላይ የዳይሬክተሮች ቦርድ አባላት እና የባንኩ ተጠባባቂ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ እሸቴ የማታ ተገኝተው ከተሳታፊዎች ለቀረቡት ጥያቄዎች፣ አስተያየቶችና ገንቢ ሀሳቦች ምላሽ ሰጥተዋል።
ተሳታፊዎች በተለይ በአገልግሎት ፍጥነት፣ በዲጂታል ባንክ አገልግሎቶች፣በብድር አቅርቦት ላይ ያላቸውን ተሞክሮ እና ችግሮች አቅርበዋል። የባንኩ አመራሮችም እነዚህን ከተሳታፊዎች
የተነሱ ጉዳዮችን በትክክል መርምረው ተገቢ እርምጃ ለመውሰድ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።
በውይይቱ ወቅት የባንኩ አመራር ከደንበኞች ጋር በቅርበት መስራት እና አጋርነትን ማጠናከር የተቋሙ ዋና ቅድሚያ ትኩረት
መሆኑን አስረድተዋል። ባንኩ በቀጣይም የተሻለ፣ ፈጣን እና ተደራሽ አገልግሎት ለመስጠት አጠናክሮ
እንደሚቀጥል ተገልጿል።
በውይይቱ ወቅት የአማራ ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ አባላት ከተሳታፊዎች በተነሱ ጉዳዮች ላይ ምላሽ የሰጡ ሲሆን፣ የአገልግሎት ጥራት እና ፍጥነት ማሻሻል የባንኩ ቀዳሚ ትኩረት መሆኑን፣ የደንበኞች ጥያቄ እና ቅሬታ በፍጥነት የሚመለስ የማኔጅመንት ስርዓት ማጠናከር፣ የዲጂታል ባንክ አገልግሎቶች ማስፋፋት እና ቴክኖሎጂ በመጠቀም ማጠናከር፣ ለንግድ እና ለኢንቨስትመንት የሚያግዙ የፋይናንስ አሰራሮች እንዲሻሻሉ እንደሚሰሩም አስታውቀዋል። ቦርዱ አክሎም ባንኩ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቀጣይነት ለመስራት እና እምነትን በተግባር ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆኑን ገልጿል።
የአማራ ባንክ ተጠባባቂ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ እሸቴ የማታ በበኩላቸው በውይይቱ ላይ በተነሱ ጉዳዮች ላይ ግልጽ እና ተግባራዊ ምላሽ የሰጡ ሲሆን፣ ባንኩ ከደንበኞች እና ከንግድ ማህበረሰቡ ጋር ያለውን ግንኙነት ማጠናከር እንደ ዋና ዓላማ መያዙን፣ የአገልግሎት ዘርፎችን በመሻሻል የደንበኛ እርካታን ማሳደግ ቁርጠኛ መሆኑን፣ የቴክኖሎጂ ልማትን በማፋጠን ፈጣን እና ተደራሽ አገልግሎት ለማቅረብ እንደሚሰራና በንግድ እና በኢንቨስትመንት ዘርፍ ያሉ ዕድሎችን ለማጎልበት የፋይናንስ አቅርቦት ላይ ትኩረት ሰጥተው እንደሚሰሩ ገልጸዋል።
ለሁለት ቀናት የተካሄደው ውይይት ባንኩ ከደንበኞቹና ከባለድርሻ አካላት ጋር የሚያገናኝ አስፈላጊ መድረክ መሆኑም ተጠቅሷል። በአጠቃላይ፣ውይይቱ የተሳካ መሆኑንና በቀጣይ በጋራ ለመስራት የተጠናከረ መሠረት እንደተፈጠረም የተገለፀ ሲሆን፣ ተሳታፊዎች ይህን ዓይነት ውይይት ቀጣይነት እንዲኖረው ጥሪ አቅርበዋል።


