ለአንድ ቀን በቆየው በዚህ ስልጠና ላይ በስነ–ምግባራዊ ውሳኔ አሰጣጥ እና በጥቅም ግጭት መከላከልና አስተዳደር ዙሪያ ሰፊ ውይይት ተደርጓል።
የአማራ ባንክ ተጠባባቂ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ተወካይ አቶ እሸቴ የማታ በመክፈቻ ንግግራቸው ባንክ በእምነት ላይ የሚቆም ተቋም መሆኑን ገልጸው፣ ይህ እምነት የሚገነባውም በታማኝነት እና በግልፅነት እንደሆነ አስገንዝበዋል። ተወካዩ እንዳሉት፡– “ታማኝነት ማለት ማንንም ሳይመለከት ትክክለኛውን ነገር መስራት ነው። አንድ ተቋም ከሙስና እና ከብልሹ አሰራር እንዲጠበቅ የላይኛው አመራር ሚና የማይተካ ነው።”
አቶ
እሸቴ አክለውም አመራሩ በአርአያነት መምራት እንዳለበት አሳስበው፣ ሰራተኞች የሚከተሉት አመራሩ የሚናገረውን ሳይሆን የሚሰራውን እንደሆነና አመራሩ ለህግና ለደንብ ተገዢ ሲሆን፣ ሙስናን የመከላከል ባህል በመላው ባንኩ እንደሚሰርፅ ገልጸዋል።
የፌደራል
ፀረ–ሙስና ተወካይ አቶ ኪዳነምህረት በበኩላቸው የጥቅም ግጭት ለሙስና መከሰት ዋነኛው መንገድ ጠራጊ መሆኑን አስረድተዋል። ማንኛውም የመንግስት ወይም የህዝባዊ ድርጅት ሰራተኛ የተሰጠውን ስልጣን በግልፅነትና በተጠያቂነት መርህ ሊጠቀም እንደሚገባ የገለፁት
ተወካዩ “በየተቋማቱ ለሙስና መከሰት ምክንያት የሚሆኑ በርካታ ሁኔታዎች ቢኖሩም፣ የጥቅም ግጭት ሙስና እንዲፈጸም ምቹ አጋጣሚዎችን ወይም መደላድልን የመፍጠር እድሉ ከፍተኛ ነው።” ብለዋል።
ስልጠናውን የሰጡት የፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ ባለሙያ ዶ/ር አወቀ አሸናፊ በበኩላቸው፣ ስነ–ምግባራዊ ውሳኔ አሰጣጥ ከጥሩ እና ከመጥፎ እንዲሁም ከተገቢ እና ተገቢ ካልሆነ የመምረጥ ሂደት መሆኑን አብራርተዋል። መሪዎች በየቀኑ የሚወስኑት ውሳኔ በተቋሙ ተልዕኮ፣ እሴቶች እና ሰራተኞች ላይ አዎንታዊ ወይም አሉታዊ ተጽዕኖ ስለሚኖረው፣ ውሳኔያቸው በመረጃ ትንታኔ ላይ ብቻ ሳይሆን በውሳኔ ሰጪው የሞራል እሴት ላይ ሊመሰረት እንደሚገባ አሳስበዋል።
በመጨረሻም የጥቅም ግጭትን ለመከላከል የጥቅም ግጭት ፖሊሲ መቅረጽ፣ ስልጠናዎችን መስጠት፣ የጥቅም ግጭት የሚፈጥሩ ሁኔታዎች ሲያጋጥሙ እራስን ከውሳኔ ማግለል፣ ሀብትን ማሳወቅና ማስመዝገብ የመሳሰሉ እርምጃዎች መወሰድ እንዳለባቸው በስልጠናው ተነስቷል።


